ንስሐ የግዕዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙ ጸጸት ነው፡፡ ጸጸትነቱ ሰው በሠራው ኃጢአት ተጸጽቶ ኃጢአቱ ይሰረይለት ዘንድ እግዚአብሔርን በሐዘን በለቅሶ ሲለምን እንጂ የጐልማሳ ሚስት ሳልቀማ፣ የሰው ገንዘብ ሳልሰርቅ ቀረሁ … በማለት የሚጸጸተው ጸጸት አይደለም፡፡
ንስሐ ለተጠመቁ ሰዎች ከጥምቀት በኋላ የተሰጠች ሀብት ናት። በጥምቀት ከእግዚአብሔር የምትገኝ የልጅነት ሁለተኛ ማዕረግ ናት፡፡ በሃይማኖት ገንዘብ ያደረግነው የመንግሥተ ሰማያት አራቦን ማለትም መግዣ ናት። ንስሐ ለሚሿት ሰዎች የተከፈተች የይቅርታ በር ናት፡፡ በንስሐ በርነት ከፈጣሪ ወደሚገኝ ቸርነት እንቀርባለን።